About DSKM

Welcome to

የርእሰ አድባራት ደብረ ሰላም ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የስብከተ ወንጌል ክፍል

ስብከት ማለት «ሰበከ፤ አስተማረ፤ አግባባ»ከሚለው የግእዝቃል የመጣ ሲሆን፣በጌታ የታዘዘ፣የእግዚአብሔርን ቃል መናገር ፣ወንጌልን ለዓለም መስበክ፣ያላመኑትን ለማሳመን መናገር፣የክርስቶስ ምስክር መሆን ማለት ነው።ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ የምሥራች፣ብርሃን፣ የጽድቅ መንገድ፣የነፍስ መስታወት፣የሕይወት ዛፍ የሆነችውን ወንጌልን አስተማረን። ሐዋርያትንም «ሑሩ ውሰተ ኩ(?)ሉ ዓለም ወስብኩ ወንጌለ ለኩ??ሉ ፍጥረት፤ ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ»ብሎ እስከ ዓለም ዳርቻ እንዲያስተምሩ ላካቸው።ማር፲፮፥፲፭ ስለኾነም ወንጌል ወደ እግዚአብሔር የሚሔዱባት የምሥራች፤ የብርሃን መንገድ፤ የነፍስ ስንቅ፤ የሐዲስ ኪዳን ተስፋ ማለት ነው፤ጌታችን ሐዋርያትን መስታወት የሆነችውን ወንጌል ይሰብኩ ዘንድ ሲልካቸው የሐዋርያት የስብከታቸው ዓላማ ኢየሱስ ክርስቶስን በዓለም መግለጥ፣ ምስክር መሆን፣አዳኝነቱን፤ ከሃሊነቱን እና ቤዛነቱን መናገር ነበር፡፡ በሐዋርያት እግር የተተኩት ሐዋርያውያን አበውም ወንጌልን በመስበክ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ በመመስከር፣ መድኀኒት ክርስቶስን በመስበክ፣ ሰውነታቸውን ለእሳት አንገታቸውን ለስለት እግራቸውን ለጠጠር ደረታቸውን ለጦር እየሰጡ ምስክርነታቸውን ፈጽመዋል አምላካዊ አደራቸው ተወጥተዋል። ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ የአበውን ፈለግ ተከትለው ትምህርተ ወንጌልን አምልተው አስፍተው አመሥጥረው ከዘመናችን አድርሰዋል። እኛም ከጌታችን ኋላም ከሐዋርያት እናከሊቃውንት ሲሰናሰል የመጣውን ትምህርተ ወንጌል ሳይከለስ ሳይበረዝ ለተተኪው ትውልድ ለማድረስ ኃላፊነትን ተቀብለናል።

የስብከተ ወንጌል ጥቅም እና አገልግሎቱ

፩.ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመግለጥ፦

ክርስቶስ «ሥጋዬን ያልበላ ደሜን ያልጠጣ የዘለዓለም ሕይወት የለውም» ብሎ በሚያስተምርበት ጊዜ አይሁድ እንዴት የሰው ሥጋ እንበላለን ብለው ይከተሉት የነበሩ በሙሉ ወደ ኋላ ሲመለሱ ሐዋርያትን እንዲህ አላቸው፤«እናንተ ደግሞ ልትሔዱ ትወዳላችሁን?»ሲላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ«ጌታ ሆይ ወደማን እንሔዳለን?አንተ የዘለዓለም የሕይወት ቃል አለህ።እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆንህ አምነናል፤ አውቀናልም» በማለት የዘለዓለም ሕይወት የሆነውን አምላክ መከተል እንዲገባ መስክሯል።ዮሐ፮፥፴ ቅዱስ ያሬድ «ወሪድየ ብሔረ ሮሜ ርኢይክዋ አእመርክዋ ወአፍቀርክዋ ለቤተ ክርስቲያን፤ ወደ ሮሜ ሀገር ወረድኩኝ ቤተ ከርስቲያንን አየኋት አወቅኋት፤ ወደድኳትም» በማለት ዕውቀት ቀርቦ በማየትና በመውደድ እንደሆነ ይናገራል።ክርስቶስን ማወቅ ማለትም ሃይማኖትን ማወቅ ማለት ነው፤ «ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖትየ ወንጌል» እንዲል (መልክአ ኢየሱስ) ስለዚህ የስብከት ዋናው ዓለማ ሃይማኖትን መስበክ ማሳወቅ በሃይማኖት በጸጋ መንፈስቅዱስ ወደ እግዚአብሔር የሚደረገውን ጉዞ ማሳየትና ሰማያዊ አቅጣጫ መስጠት ነው፡፡

፪ ክርስቶስን ለመምሰል፦

Educating the Young, Guiding the Community

ቅዱስ ጳውሎስ«ተመሰሉ ኪያየ በከመ አነ እትሜሰሎ ለክርስቶስ፤እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እናንተም እኔን ምሰሉ» በማለት፩ኛ ቆሮ ፲፩ ፥ ፩ክርስቶስን እንድንመስለው ይነግረናል።ስብከት ስንል በትሕትና፤ በትግዕሥት፤ በመከራና ክርስቶስን በመምሰል የሚገለጥ ሕይወት ይኖረን ዘንድ የምንማርበት ነው። ሃይማኖታችን የምናጸናበት ምግባራችንን የምናቀናበት መለኮታዊ ጸጋ ነው። ምክንያቱም ምግባራችን የቀና ሃይማኖታችን የጸና ካልሆነ ክርስቶስን መምሰል አንችልምና።ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ «ሃይማኖት ዘእንበለ ምግባር ምውት ይእቲ። ሃይማኖት ያለምግባር የሞተ ነው» ብሎ እንዳሳሰበን ሃይማኖትና ምግባር አስተባብረን መያዝ ይገባል፤ ለዚህ ልዩ ጸጋ ለመታደል ደግሞ ስብከተ ወንጌል የግድ ያስፈልጋል።

፫ የቅዱሳንን ፍኖት ለመከተል፦

እግዚአብሔር ያከበራቸው የመረጣቸው እነርሱም መርጠውት ከዘመድ ባዳ ከሀገር ምድረ በዳይሻላል ብለው ዳዋ ጥሰው ጤዛ ልሰው ደንጋይ ተንተርሰው ድምፀ አራዊቱ ግርማ ሌሊቱ ፀብአ አጋንንቱ ሳያስፈራቸው ስሙን ብቻ ይዘው የወጡትን እናመሰግናቸው እናከብራቸዋለን።ለዚህ ነው ቅዱስ ጳውሎስ«የኑሯቸውን ፍሬ እየተመለከታችሁ ዋኖቻችሁን ምሰሉ»ያለው።በሕጉና በትእዛዙ ጸንተው በጾም በጸሎት ተወስነው ዓለምን ድል ያደረጉ በተጋድሎ ላይ ያሉትም ሕያው ወንጌል ተንቀሳቃሽ እና ሕያው ወንጌል ማለት ናቸውና። በወንጌል ላይ የተጻፈውን የሚተረጉሙ፣ አይቻልም የምንለውን ችለው፣ በተግባር ያሳዩን ናቸው።ጌታችን በወንጌሉ «እውነት እውነትእላችኋለሁ በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፤ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል» በማለትተናግሯል፡፡ዮሐ፲፬፥፲፪ እርሱ እንደተሰደደ ተሰደው፣እንደተራበ ተርበው፣እንደተገረፈ ተገርፈው እንደተሰቀለ ተሰቅለው የክርስቶስን ሕይወት በተግባር የተረጎሙ፤ድውይ እንደፈወሰ ፈውሰው ሙት እንዳስነሣ አስነሥተው በተአምራቱ የተሳተፉ፤ በቅድስና በንጽሕና የሚኖሩትን ቅዱሳንን እናውቅ ዘንድ እንዲሁም አሠረ ፍኖታቸውን እንከተል ዘንድ ስብከተ ወንጌል ያስፈልጋል።

በነቢዩ በኢሳይያስ ላይ አድሮ«ወደ አባታችሁ ወደ አብርሃም ወደ ወለደቻችሁ ወደ ሣራ ተመልከቱ» እንዳለን ፶፩ ፥ ፪ ቅዱሳን ወንጌልን የምንረዳባቸው የምናውቅባቸው እግዚአብሔርን የምናይባቸው መነጽር ማለት ናቸው። ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በርካታ መምህራንም እያስተማረች በየቦታው ስታሰማራ ኖራለች፤ ወደፊትም ይህንን ተልእኮዋን ትቀጥላለች፤ ምክንያቱም ስብከተ ወንጌል ቃለ እግዚአብሔርን ለማስተማር ብቻ ሳይኾን የሰውን አእምሮ ለማልማት እና መልካም አስተሳሰብን ለመገንባት የሚያስችል ዋነኛው የቤተክርስቲያን መሣሪያ ነውና፡፡

 

በስብከተ ወንጌል ያሉ ክፍሎች ዝርዝር መዋቅርና ተግባራት

፩. የጉባኤ አስተባባሪ ክፍል

ይህ ክፍል ጠቅላላውን የጉባኤ ዝግጅት፣ የስብከት መርሐግብር ስምሪትንና መንፈሳዊ ጉባኤያትን በበላይነት የሚያቀናጅ ዋና ሞተር ክፍል ነው።

1.የስብከት መርሐግብር ማውጣት፦ ሳምንታዊ፣ ወርሃዊና ዓመታዊ የሰንበትና የዓውደዓመት ጉባኤያትን መርሐ ግብር ያዘጋጃል ይመራል።

2.መምህራንንና ዘማርያን መጋበዝና ማሰማራት፦ በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ወቅታዊ ትምህርት ሊሰጡ የሚችሉ፣ ተደማጭ የኾኑ፣ በሰብእናቸውና በአገልግሎታቸው በማኅበረሰቡ ዘንድ የተመሰከረላቸውን መምህራን፣ ሊቃውንትና ዘማርያንን ይጋብዛል።

3. የጉባኤ ቦታና ቁሳቁስ ማዘጋጀት፦ ለጉባኤ የሚያስፈልጉ የድምፅ (Sound System) የጽዳት ሥራዎችን ከሚመለከታቸው ክፍሎች ጋር በመሆን ማስተባበር፤ ቀደም ብሎ ተገኝቶ መድረኩንና ወንበሩን በአጠቃላይ የጉባኤውን ቦታ ያዘጋጃል።

4. ለሕዝቡየጉባኤ ጥሪ ማዘጋጀት፦ ታላላቅ ጉባኤያት ከመካሄዳቸው በፊት ለምእመናን ጥሪ ማስተላለፍ፣ በራሪ ወረቀቶችን ፖስተሮችን የማስታወቂያ ቪዲዮችን ያዘጋጃል ያሠራጫል።

5. የሰባክያንና የመምህራን መዝገብ መያዝ፦ የሰባክያንን አድራሻ ይመዘግባል[ በየጊዜው ያስታውሳል። የተጋበዙትን መምህራንን ካሉበት ይቀበላል በተዘጋጀላቸው ማረፊያ ቦታ ያደርሳል አስፈላጊውን እንክብካቤ ያደርጋል፤ አገልገሎታቸውን ሲጨርሱ ይሸኛል።

6. በዕለቱ የሚቀርበውን መርሐ ግብር መንደፍ፦ በጉባኤያቱ የሚቀርቡትን የትምህርት፣ የስብከትና የዝማሬ መርሐ ግብራትን መቼት (ሰዓትና ቦታ)፣ ይዘትና ዓይነት በጥናት ላይ ተመስርቶ ይቀርጻል ይመራል ይቆጣጠራል።

7.የድምፅና የምስል ጥራትን መከታተል፦ የጉባኤው ድምፅ ጥራት ያለውና ለአድማጭ የማይረብሽ መሆኑን መከታተል፣ እንዲሁም ለቪዲዮና ለኦዲዮ ቅጂዎች ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል።

8.የበጀትና ወጪ ማቀድ፦ ለጉባኤያት ማካሄጃ (ለምሳሌ ለማስታወቂያ፣ ለጋበዟቸው መምህራን መጓጓዣና ማስተናገጃ) የሚያስፈልገውን በጀት አስቀድሞ ያዘጋጃል።

9. የጉባኤ መገምገሚያ ሥርዓት፦ ከጉባኤያት በኋላ የምእመናንን አስተያየትና ተሳትፎ በመሰብሰብ ለቀጣይ ሥራዎች ማሻሻያ እቅድ ያቀርባል።

10.የአማራጭ መድረኮችን ማዘጋጀት፦ እንደ አመቺነቱና እንደ ሁኔታው ምእመናንን በአካል የሚያሳታፉ (In-person) ወይም በቴክኖሎጂ የታገዙ የቨርችዋል ልዩ ልዩ ጉባኤያትን ያዘጋጃል።

11 ምእመናንን በአገልግሎት ማሳተፍ፦ ኹሉም ምእመን በደብሩ በሚሰጠው አገልግሎት ውስጥ በመማር ሂደት እንዲያልፍ፣ እንደ ጸጋውና እንደ ሙያው ደግሞ በማገልገል የራሱን ሱታፌ እንዲያበረክት ያደራጃል ማስተናገጃ መንገድ ይፈጥራል።

፪. የወጣቶች ትምህርት አስተባባሪ ክፍል

ይህ ክፍል ወጣቶች (ከአዳጊ እስከ ኮሌጅ መግቢያ ዕድሜ ያሉትን) ከመንፈሳዊ ሕይወት በተጨማሪ ከወቅታዊና ስነ ልቦናዊ ተጽዕኖዎች የሚጠብቅ ትምህርት ላይ  የሚያተኩር ክፍል ነው።

1.ወቅታዊና ስነልቦናዊ ትምህርቶች፦ ወጣቶችን ከሱሰኝነት፣ ከግብረገብነት መበላሸትና ከቴክኖሎጂ ተጽዕኖ የሚጠብቁ መንፈሳዊና ስነ ልቦናዊ ስልጠናዎችንና ትምህርቶችን ያዘጋጃል።

2.የውይይት መድረኮች (Forums)፦ ወጣቶች የሚያጋጥሟቸውን ጥያቄዎችና ጥርጣሬዎች በነፃነት የሚያነሱባቸውና ምላሽ የሚያገኙባቸውን የክብ ጠረጴዛ ውይይቶች ያደራጃል።

3.የክህሎትና የበጎ ፈቃድ ልማት፦ ወጣቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ የአመራርነትና የባሕርይ ግንባታ ስልጠናዎችን መስጠት፣ በበጎ አድራጎት ሥራዎች ያሰማራል።

4.የኪነ ጥበብና የሚዲያ አጠቃቀም፦ ወጣቶች በኪነ ጥበብ (በግጥም፣ በቲያትር) እና በዲጂታል ሚዲያ በመጠቀም ወንጌልን የሚሰብኩበትን መንገድ ያመቻቻል።

5.የምክር (Counseling) አገልግሎት፦ በማንነት ቀውስና በተለያዩ ማኅበራዊ ጫናዎች ውስጥ ለሚገቡ ወጣቶች መንፈሳዊና ስነልቦናዊ የምክር አገልግሎት እንዲያገኙ ያደርጋል።

6.የክህሎት ማሳያ መድረኮችን ማዘጋጀት፦ ወጣቶች ያላቸውን የስዕል፣ የጽሑፍ፣ የቴክኖሎጂና የፈጠራ ክህሎት ከመንፈሳዊ ሕይወት ጋር አስተሳስረው የሚያሳዩበትን ዓመታዊ ኤግዚቢሽን ያዘጋጃል።

7.የአቻ ለአቻ (Peer-to-Peer) ማማከር ሥርዓት፦ በባሕርይና በትምህርት የበሰሉ ወጣቶች ለአነስተኛ ታዳጊዎች አርአያና መካሪ (Mentor) የሚሆኑበትን ሥርዓት ይዘረጋል።

8.የንዑሳን ኮሚቴዎች ምሥረታ፦ በወጣቶች ስር የንባብ፣ የቅርስ ጥበቃ፣ የማኅበራዊ ሚዲያና የበጎ አድራጎት ንዑሳን ቡድኖችን በማዋቀር የኃላፊነት ስሜትን ያሳድጋል።

9.የወላጆችና የወጣቶች የጋራ መድረክ፦ በወላጆችና በልጆቻቸው መካከል ያለውን የአስተሳሰብ ልዩነት የሚያጠብቡ የጋራ የውይይት ቀናትን ያሳድጋል።

፫. የአዋቂዎች ተከታታይ ትምህርት አስተባባሪ ክፍል

ይህ ክፍል በዕድሜና በማኅበራዊ ኃላፊነት የበሰሉ አዋቂዎችን (ባለትዳሮችን፣ ወላጆችንና በሥራ ዓለም ያሉትን) መሠረት ያደረገ ጥልቅና ቀጣይነት ያለው ትምህርት የሚሰጥበት ክፍል ነው። የሥራውም ዝርዝር እንደሚከተለው ይቀርባል፦

1.ሥርዓተ ትምህርት ማዘጋጀት፦ ለአዋቂዎች የሚመጥን፣ በደረጃ የተከፋፈለ (ከመሠረታዊ እስከ ጥልቅ የሃይማኖት ምስጢራት) ተከታታይ የትምህርት ሥርዓት ይነድፋል።

2.የቤተሰብና የትዳር ሕይወት ትምህርት፦ የትዳር መሠረቶች፣ የልጆች አስተዳደግ፣ በክርስቲያናዊ ሥነምግባር ቤተሰብን መምራት በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ሴሚናሮችን ያዘጋጃል።

3.የንባብና የምርምር ባህል ማሳደግ፦ አዋቂዎች መጻሕፍትን የሚያነቡባቸውንና የሚወያዩባቸውን የንባብ ክለቦች (Book Clubs) ያቋቁማል።

4.የምዝገባና የክትትል ሥርዓት፦ በተከታታይ ትምህርቱ ላይ የሚሳተፉ ሰዎችን መዝገብ መያዝ፣ መገኘታቸውን መከታተልና በትምህርቱ ማጠናቀቂያ ላይ የምስክር ወረቀት ያዘጋጃል።

5.የመማሪያ ሞጁሎችና መጻሕፍት ማዘጋጀት፦ ለተከታታይ ትምህርቱ የሚሆኑ መጻሕፍትን ወይም አጫጭር የትምህርት ማጠቃለያዎችን (Handouts) አስቀድሞ ያዘጋጃል ያሠራጫል።

6.የምዘናና ፈተና ሥርዓት መዘርጋት፦ ትምህርቱ ዝም ብሎ መስማት ብቻ እንዳይሆን፣ በየክፍለ ጊዜው ማጠናቀቂያ ላይ ቀለል ያሉ የጽሑፍ ወይም የቃል ጥያቄዎችንና የቡድን ሥራዎችን ያዘጋጃል።

7.የመልሶ ማስተማር ሥርዓት፦ በትምህርቱ ከፍተኛ ውጤትና ፍላጎት ያሳዩ አዋቂዎችን መርጦ ሌሎችን መልሰው ማስተማር የሚችሉበትን የአሠልጣኝነት ሥልጠና ይሰጣል።

8.የግንዛቤና የሥልጠና መርሐ ግብር ማዘጋጀት፦ ወላጆች ካለባቸው የኃላፊነት ጫና፣ የመሸማቀቅና የባይተዋርነት ስሜት እንዲወጡ የሚያግዙ ልዩ ሥልጠናዎችንና ትምህርቶችን ያደራጃል።

9.የልምድ ልውውጥ መድረኮችን መፍጠር፦ ወላጆች እርስ በርሳቸው ተሞክሮ የሚለዋወጡባቸውን የውይይት መድረኮች ያዘጋጃል።

10.የመንፈሳዊና ስነ ልቦናዊ ድጋፍ መስጠት፦ ወላጆች በተስፋ መቁረጥ መንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዳይዝል ተከታታይ የጸሎትና የሕይወት ማበረታቻ መርሐ ግብራትን ይነድፋል።

11.የአፈጻጸም መመሪያ ማውጣት፦ የሥልጠናውን ዝርዝር ይዘት፣ አቀራረብና የአፈጻጸም ጊዜ ሰሌዳ በጉባኤና በውይይት ዳብሮ እንዲጸድቅ ያደርጋል።

፬. የኮሌጅ ተማሪዎች ክትትል አስተባባሪ ክፍል

ይህ ክፍል ከቤተሰብ ርቀው በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት (ኮሌጅ/ዩኒቨርሲቲ) ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎችን በማንነታቸው እንዲጸኑና እርስ በርሳቸው እንዲደጋገፉ የሚሠራ ልዩ ክፍል ነው።

1.የተማሪዎች መረጃ ቋት፦ ከአካባቢው ወደ ተለያዩ ኮሌጆች የሚሄዱትንና ወደ አካባቢው ኮሌጆች የሚመጡ አዲስ ተማሪዎችን መረጃ በሥርዓት መዝግቦ ይይዛል።

2.የግቢ ጉባኤያት ድጋፍና ክትትል፦ በየኮሌጆቹ ውስጥ ካሉ የግቢ ጉባኤያት መሪዎች ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት በመፍጠር የመጻሕፍት፣ የባለሙያ ድጋፍ ያደርጋል።

3.ከሳይንስና ፍልስፍና ጋር የተያያዙ ማብራሪያዎች፦ በኮሌጅ ደረጃ የሚነሡ የሳይንስና የፍልስፍና ጥያቄዎች እምነትን እንዳያናጉ፣ ምሁራንን በመጋበዝ ምላሽ ሰጪ የሆኑ ሴሚናሮችንና ሲምፖዚየሞችን ለተማሪዎች ያዘጋጃል።

4.የዕረፍት ጊዜ መርሐ ግብራት፦ ተማሪዎች በዕረፍት (ክረምት) ጊዜያቸው ወደየአካባቢያቸው ሲመለሱ በስብከተ ወንጌል መዋቅሩ ውስጥ ገብተው እንዲያገለግሉና ልዩ ልዩ ሥልጠናዎችን እንዲወስዱ ኣደርጋል።

5.የሽግግርና የሥራ ዓለም ዝግጅት፦ ትምህርታቸውን የሚያጠናቅቁ ተማሪዎችን መርቆ መሸኘትና ወደ ሥራው ዓለም ሲገቡ ክርስቲያናዊ ሙያዊ ሥነ ምግባርን (Professional Ethics) የተከተለ አኗኗር እንዲኖራቸው ይመክራል።

6.የግቢ ጉባኤ መሪዎች ጉባኤ (Focus Group)፦ በየወሩ ወይም በየሴሚስተሩ ከየካምፓሱ የግቢ ጉባኤ መሪዎች ጋር በአካል ወይም በኦንላይን (Zoom/Telegram) በመገናኘት ያሉባቸውን ችግሮች ይሰማል።

7.የማቴሪያልና የመጻሕፍት ባንክ ማቋቋም፦ በኮሌጅ ተማሪዎች ዘንድ የሚነሱ የነገረ መለኮት፣ የታሪክና የሳይንስ ጥያቄዎችን የሚመልሱ መጻሕፍትን በዲጂታል (PDF) እና በሃርድ ኮፒ አደራጅቶ ለተማሪዎች ያደርሳል።

8.የአእምሮ ጤናና የጭንቀት ማስታገሻ መርሐ ግብር፦ በፈተና ወቅትና በተለያዩ ማኅበራዊ ጫናዎች ምክንያት ተማሪዎች ለሚገጥማቸው የአእምሮ ውጥረት (Academic Stress) የምክርና የጸሎት ድጋፍ ያደርጋል።

9.የተመራቂዎችና የሥራ ፈላጊዎች መድረክ፦ ትምህርታቸውን የጨረሱ ተማሪዎች ከሥራ ዓለም ጋር እንዲተዋወቁ፣ ቀደም ብለው በሥራ ዓለም ካሉ ታላላቆቻቸው ጋር የሚያገናኝ «የሥራ መርሐ ግብር ሴሚናር» ያዘጋጃል።

፭. የምክር አገልግሎት ክፍል

ይህ የምክር አገልግሎት ክፍል መፍቀሬ ትዕግሥት ኢዮብ «ሕይወት በምድር ላይ ብርቱ ሰልፍ ናት» ብሎ እንደተናገረው በብዙ ፈተና እና ውጣውረድ በተከበበች ዓለም ላይ ስለምንኖር በተለያየ ምክንያት የሰው ልጅ ለጭንቀት ለመንፈስ መረበሽ እና ለተስፋ መቁረጥ ሊጋለጥ ይችላል፤ስለዚህ ምእመናን በግል ኑሯቸው በትዳራቸው በሥራቸው በጤናቸው በልዩ ልዩ ችግሮች ምክንያት ተቸግረውና ተጨንቀው ሲመጡ እንዲረጋጉ ተስፋ ሳይቆርጡ የገጠማቸውን ችግር በእግዚአብሔር ኀይል እንዲወጡት የሚያደርግ የማጽናናት የማጠናከርና የማበረታታት አገልግሎት የሚሰጥበት የአገልግሎት ዘርፍ ነው፤በዚህ መርሐ ግብር በርካታ የተጨነቁ ያዘኑ ምእመናን መጥተው በቃለ እግዚአብሐር በምክር ተጽናንተው የሚመለሱበት የተጣሉ የሚታረቁበት ከጭንቀታቸው የሚረጋጉበት ከኀዘናቸው የሚጽናኑበት እና ለዕንቆቅልሻቸው መፍትሔ የሚያገኙበት ወሳኝ አገልግሎት ነው።

ዘወትር በየሳምንቱ በእነዚህ ቀናት የምክር አገልግሎትይሰጣል፦

ረቡዕ 400 PM እስከ 500 PM ( ከሰዓት በኋላ 10:00 – 11:00)

ዐርብ 400 PM እስከ 500 PM ( ከሰዓት በኋላ 10:00 – 11:00)

  • ምክር ለማግኝት ቀጠሮ መያዢያ ፎርም ሊንክ

፮ የሚዲያ ስርጭት ክፍል

እንደሚታወቀው ዘመኑ የዲጂታል ዘመን እንደመኾኑ መጠን ወጣቱም አዛውንቱም የማኅበራዊ ሚዲያ ምርኮኛ ከኾነ ብዙ ዓመታትን አስቆጥረናል። የማኅበራዊ ሚዲያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ ተፅዕኖ ያለው መኾኑ ግልጽ ነው።በማኅበራዊ ሚዲያ ሰዎች ልዩ ልዩ ሐሳቦችን መረጃዎችን ዕውቀቶችንና የግል ልምዶች ይለዋወጡበታል፣ ይህ ሲባል አሉታዊ ተጽዕኖው ሳይዘነጋ በዓለም ዙሪያ ባሉ ሰዎች መካከል ማኅበረሰባዊ መስተጋብር የባህል ግንዛቤን እና ትብብርን ለማሳደግ በጎ አስተዋጽኦ ያደርጋል። በማኅበራዊ ድረ ገጾች ከሚቀርቡት አዎንታዊ ጉዳዮች አንዱ ወጣቶች ሐሳባቸውን እንዲገልጹ እና በቀላሉ ለሌሎች እንዲያካፍሉ ዕድል የሚሰጥ መሆኑ ነው።

ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ይህን ትውልድ ለማግኘት የዘመኑን ቴክኖሎጂ ተጠቅማ ስብከተ ወንጌልን በማኅበራዊ ሚዲያ የማዳረስ ግዴታ ይኖርባታል።የማኅበራዊ ሚዲያ አገልግሎት በዘመናችን ተመራጭ ያደረገው ብዙ ምክንያቶች ቢኖሩትም በዋናነት ግን በቀላሉ ተደራሽ መኾኑና በፍጥነት የሚዘጋጅና የሚሠራጭ ነው፤በትንሽ ወጪ የሚሠራ ነው፤ቦታና ጊዜ ሳይገድበው ቶሎ ጥቅም ላይ የሚውል ነው፤በእነዚህና በመሳሰሉ ምክንያት ማኅበራዊ ሚዲያ ትውልዱን ለማስተማር ተመራጭ መንገድ መኾኑ አከራካሪ አይደለም፤በተለይ ማራኪ በኾነ መንገድ ከተዘጋጀ የአንባብያንን እና የሰማዕያንን ተሳትፎ እጅግ የሚያበረታታ መንገድነው።

ማኅበራዊ ሚዲያ የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ለማስተዋወቅ እና የትምህርት እና የሥልጠና ዕድሎችን ለማቅረብ መጠቀም ይቻላል። ማኅበራዊ ሚዲያ ለበጎ አድራጎት እና ለመንፈሳዊ ፕሮጀክቶች እርዳታ እና ልገሳ ለማሰባሰብ ውጤታማ መንገድ ነው። የማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮች ኅብረተሰቡን በተለያዩ ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ለማስተማር ለምሳሌ ስለ ቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ጉዳዮች ስለሥርዓተ አምልኮና ስለወጣቶች ሕይወት ግንዛቤ ለማስጨበጥ በእጅጉ ይጠቅማል። ስለኾነም ይህ ንዑስ ኮሚቴም የተለመዱትን የቤተ ክርስቲያናችንን የትምህርት እና የስብከት ማቅረቢያ መንገዶችን እንዲሁም የተለያዩ  ድህረ ገጾችን ተጠቅሞ በዘርፍ በዘርፍ ለተለያዩ የቅስቀሣ ዘመቻ አገልግሎቶች ያደራጃል ያሰራጫል።

በየሳምንቱ በእነዚህ ቀናት የስብከተ ወንጌል የሚዲያ ስርጭት ይከናወናል

ረቡዕ 600 PM እስከ 800 PM ( ከሰዓት በኋላ 12:00 – 2:00)

ዐርብ 600 PM እስከ 800 PM ( ከሰዓት በኋላ 12:00 – 2:00)

የዩትዩብ ሊንክ ፦